የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ የክፍያ መንገዶች ላይ የታሪፍ ማሻሻያ ሊያደርግ መሆኑን አስታወቀ፡፡

የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ላለፉተ 8 አመታት ቀልጣፋና ዘመናዊ በሆነ መልኩ ያልተቋረጠ የ24/7 የክፍያ መንገድ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ኢንተርፕራይዙ የሀገራችን ዋነኛ የወጪ እና ገቢ ንግድ መስመር የሆነውን የአዲስ – አዳማ ፣ በጅቡቲ መስመር ምስራቃዊ የሀገራችንን ክፍል የሚገኘውን የድሬደዋ – ደወሌ እንዲሁም የምስራቅ አፍሪካ የትራንስ ሀይዌይ መንገድ አያያዥ የሆነውን የሞጆ – ባቱ የፈጣንና የክፍያ መንገዶችን ተረክቦ በማስተዳደር ላይ ይገኛል፡፡ መንገዶቹ  የገቢ-ወጪ ንግድ ኮሪደር አካል እንደመሆናቸው የሎጂስቲክ ስርአቱን ውጤታማነትን በማሳደግ ኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና አካባቢያዊ ፋይዳቸው የጎላ ነው። ኢንተርፕርይዙም ለሚሰጠው አገልግሎት ተመጣጣኝ የክፍያ ታሪፍ መተግበሩ ለአገልግሎቱ አዋጭነት እና ዘላቂነት ወሳኝ ሚና ይኖረዋል።

የፈጣን የክፍያ መንገድ የአገልግሎት ክፍያ ታሪፍ እሳቤ ተሽከርካሪዎች የፍጥነት መንገድን ሲጠቀሙ ከሚያገኙት የጉዞ ጊዜ ቅናሽ ፤የነዳጅ ወጪ ቅናሽ ሌሎች የተሽከርካሪ ማንቀሳቀሻ ወጭዎች ቅናሽ እንዲሁም ከመንገዱ ዘመናዊነት ጋር ተያይዞ በፍጥነት መንገዱ ላይ ማሽከርከር ከፍተኛ የሆነ ምቾት እና የደህንነት ጥቅም ማግኘታቸው የሚጠቀስ ነው፡፡ በመሆኑም የታሪፍ ማሻሻያው ደንበኞች ከፍጥነት መንገዶቹ የሚያገኙትን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እንዲሁም የኦፕሬሽን እና የመንገድ ሀብት ጥገና  ወጪ እድገትን ታሳቢ ያደረገ እና ተቋማዊ የፋይናንስ አቅምን ለማሳደግ የታለመ ነው።

ታሪፉ ተሽከርካሪዎች በተጓዙት ርዝመት እና በአራት የክፍያ መደቦች (አነስተኛ ተሽከርካሪዎች (ምድብ አንድ)፣ መለስተኛ ተሽከርካሪዎች (ምድብ ሁለት)፣ የጭነት ተሽከርካሪዎች  (ምድብ ሦስት) እና ከባድ እና ተሳቢ ተሽከርካሪዎች  (ምድብ አራት)) ይከፈላል።

ኢንተርፕራይዙ ከጥቅምት 22/2015 ጀምሮ አዲሱን የክፍያ ታሪፍ ማሻሻያ ይተገብራል፡፡ በመሆኑም ደንበኞች የታሪፍ ለውጥ መኖሩን አውቃችሁ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት እንድታደርጉ እያሳወቅን ስለታሪፍ ለውጡ ዝርዝር ማብራሪያ ከዚህ በታች በተገለፁ የተቋሙ ማህበራዊ ትስስር ገፆች መመልከት የምትችሉ መሆኑን በአክብሮት እንገልፃለን ፡፡

ድረገጽ፡- etre.com.et ቴሌግራም፡- https://t.me/etrechannel

ፌስቡክ፡-facebook.com/etre ስልክ፡- አዲስ-አዳማ +251-114171717

ሞጆ-ባቱ፡- +251-228125889 ድሬደዋ ደወሌ፡- +251-258903797 አጭር ነፃ መስመር 8808