================================
ኢክመኢ [ETRE ሐምሌ 27/2018 ዓ.ም]
በዛሬው ዕለት «ተስፋን እንትከል» በሚል መሪ ቃል በተካሄደው የአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ 28,800 ችግኞችን በ163ሺ ካሬ ቦታ ላይ በመትከል ለአገራዊው የአረንጓዴ ልማት እና የአካባቢ ጥበቃ ጥረት የበኩሉን አስተዋጽኦ አበርክቷል።
በመርሃ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሙስጠፋ አባሲመል ባስተላለፉት መልዕክት፣ የዛፍ ተከላ የትውልድን ህይወት የሚጠብቅ፣ የአካባቢን ሥነ-ምህዳር የሚያሻሽልና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቀነስ ከፍተኛ ሚና ያለው ተግባር መሆኑን ገልጸው፣ ተቋሙም እንደ ሀገራዊ ተቋም በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ ያለውን ተሳትፎ ወደፊትም በተከታታይ እንደሚያጠናክር አስገንዝበዋል።
በዕለቱ ሁሉም የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ሠራተኞች በተመደቡባቸው የስራ አካባቢዎች በመገኘት ችግኞቹን በንቃትና በትብብር ተክለዋል። ይህም የተቋሙ ሠራተኞች ለአካባቢ ጥበቃና ለሀገራዊ ልማት ያላቸውን ኃላፊነት በተግባር ያሳየ ተሳትፎ ነበር።
እንደዚሁም የሌሎች መንግስታዊና የግል ተቋማት ሠራተኞች በክፍያ መንገዱ ዳር ላይ በመሰማራት ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ችግኝ በመትከል ለመርሃ ግብሩ ስኬት አስፈላጊ አስተዋጽኦ አድርገዋል። የተቋማቱ የጋራ ተሳትፎ የአካባቢ ጥበቃ እና የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች በትብብር ሲከናወኑ የተሻለ ውጤት እንደሚያስገኙ አሳይቷል።
የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ከዋና ተልዕኮው በተጨማሪ ለአካባቢ ጥበቃ፣ ለአረንጓዴ ልማት እና ለማህበራዊ ኃላፊነት መወጣት የሚያግዙ መርሃ ግብሮችን በቀጣይነት በማከናወን ለሀገሪቱ ዘላቂ ልማት የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ ይቀጥላል።
የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ
ደህንነትዎ የክብር ስማችን ነው!!

